
እነሆ Ethiobalkan Episode II.
ጤና ይስጥልኝ ፥ ጤና ይስጥልኝ ፥ ጤና ይስጥልኝ ኣድማጮቼ!
በክፍል አንድ ፕሮግራማችን በአንድ አገር ውስጥ የርስ በርስ ጦርነት እንዴት ማንም ሳይፈልገው ይቀሰቀሳል? በሚል ጥያቄ ጀምረን የዛሬ 27 አመት ገደማ የዩጎዝላቪያ አብዛኛው ህዝብ ሳይፈልገውና ሳያስበው አሸናፊ ወዳልተገኘለት የለየለት ጦርነት ሃገሪቷ ልትገባ እንደቻለች፥ አልፎም ከሁለተኛው የአለም ጦርነት ወዲህ በአውሮፓ ታይቶ የማያውቅ እልቂት፥የሰዎች ጭካኔ፥የዘር ማጥፋትና የዘር ማፅዳት በሰፊው እንደተካሔደ፥ ዩጎዝላቪያም እንደ ሃገር መቆም እንደተሳናትና ልትፈርስ እንደቻለች አንስተን ነበር።
በዚያ ወደ 11 ዓመት በፈጀ ተከታታይና የተወሳሰበ ግጭትም ወደ 2መቶ ሺህ (በአብዛኛው ሰላማዊ ሰዎች) በአሰቃቂ ሁኔታ እንዲሞቱ፥ ብዙዎችም ደብዛቸው እንዲጠፋ እንደተፈረደባቸው። ከ4 ሚሊዮን በላይ የሚሆኑ ነዋሪዎቿም እስከዛሬ ላልተቋጨ ስደት እንደተዳረጉም አንስተን ነበር።
ታድያ ሁኔታውን ከስረመሰረቱ ለመረዳት ያስችለን ዘንድም የዩጎዝላቪያን የቀድሞ ታሪክ፥ የፌደሬሽኑን አመሰራረት፥ አጠቃላይ የህዝቡንና በውስጧ ተዋህደው የሚኖሩትን የተለያዩ ብሄረሰቦች በጨረፍታ ከዳሰስን በሗላ የማርሻል ቲቶን ከዚህ አለም በሞት መለየት አውስተን ነበር ያቆምነው።
ታዲያ በዚያው ክፍልም የባልካኑን ቀውስ እንዳቀርብላችሁ ምን እንደገፋፋኝም ጠቅሼ ነበር። በክፍል አንድ እንዳነሳነው የቀድሞዋ ዩጎዝላቭያ እንደዚያ ልይቶላት ከመፍረሷ በፊት የነበሩት የሃገሪቷ አጣቃላይ ሁኔታዎች፥ የፖለቲካ ንትርክና እቅጣጫ ማጣት፥ አነስተኛም ቢሆን እዚህም እዚያም የሚነሱ ግጭቶችና አጠቃላይ የኢኮኖሚ ተግዳሮቶች ከእያንዳንዷ የሃገራችን የወቅቱ ሁኔታ ጋር በአብዛኛው ተመሳሳይነት እንዳላቸው፥
ይህም ለረጅም ጊዜ ሲያሳስበኝ እንደቆየ፥ ሆኖም ከቀደምት ታሪኮች የሚማር ብልህ ነው እንደሚባለው የባልካኑን ቀውስ እንዲሁም ሌሎችን በመመርመር በግዜ ከተማርንባቸው የወቅቱን የሃገራችንን ሁኔታና ወደፊት ሊከሰቱ የሚችሉ ብዙ በአሁኑ ግዜም እያየናችው ያሉ ተመሳሳይ ምልክቶች ወደ አይቀሬና መጥፎ እጣ ፈንታነት ከመለወጣቸው በፊት ለማመላከት ይረዳል ብዬ በማመኔ እንደሆነ አንስቼላችሁ ነበር።
በዚሁ ስሜትና አላማ ነው እንግዲህ ክፍል ሁለት ኢትዮባልካን ፕሮግራምን የማቀርብላችሁ።
በዚህ ክፍል ከማርሻል ቲቶ ሞት በሗላ የነበረችውን ዩጎዝላቪያን እያየን በዚያውም ለዩጎዝላቪያ ግብአተ መሬት መብቃት እንዲሁም ለተከሰተው ከፍተኛ የሰብዐዊ ቀውስ፥ የህዝብ እልቂትና ስቃይ ጉልህ ሚና የተጫወቱ ዋና ተዋናዮችንና ገፊ ተግዳሮቶችን እንቃኛለን።
አስተያየት ወይም ምክር ካላችሁ ይህ ፓድካስት በfacebook, anchor podcast, google podcast, spotify, radio public, breaker audio, youtube እና በSoundcloud ላይም ስለምታገኙት በአስተያየት መስጫቸው ላይ ሃሳብዎን ቢያሰፍሩ በጣም ደስ ይለናል።